Wednesday 11 December 2013

ምኒልክ ማነው ?


ምኒልክ ማነው ? ”


(የአንድ ተቋም ሰልጣኞች ጥያቄ)

በአዲስ አበባ ፒያሳ አካባቢ የጋዜጠኝነት ስልጠና የሚሰጥ ተቋም አለ፡፡ አሰልጣኙ ስለ ቃለ መጠይቅ (ቃለ ምልልስ) እያስተማሩ የተለያዩ ምሳሌዎች እያቀረቡ ያስረዳሉ፡፡ በመካከል ‹‹ ለመሆኑ አፄ ምኒልክ የት ተወለዱ? ›› ብለው ጠየቁ ለተግባር ልምምድ መድረክ ላይ ለነበሩት ሰልጣኞች ቡድን ውስጥ መልስ የሚሰጥ አልተገኘም፤ ከ35 በላይ ለሆኑኑት በክፍሉ ውስጥ ለሚገኙት ጥያቄውን ደገሙት ወዲያው ‹‹ የቤት ስራ ይሁን›› ብለው ወጡ፡፡ ከ3 ቀናት በኃላ ገና እንደገቡ ሁለት ሰልጣኞች እጅ አወጡ ‹‹ ሳይቀድሙን…….. ›› ብለው ያሰቡ ይመስላል፡፡ ለአንዱ ዕድል ሰጡ ‹‹ ለመሆኑ ምኒልክ ማነው ? ›› ብሎ የቤት ስራ የነበረው ለመምህሩ የክፍል ስራ አድርጎ ጠየቀ ፡፡ መምህሩም እየተገረሙ ወደ አንደኛው እጅ አውጥቶ ወደነበረው    ‹‹አንተስ መልስ ነው ? ›› አሉት፡፡ ‹‹ አይደለም የእኔም ጥያቄ ይሄው ነበር ›› አለና አረፈው፡፡
#መጠየቅ ያደርጋል ሊቅ; ይባላል በጎ ነው፡፡ ግን ስለ አፄ ምኒልክ ጽሑፍ@ ነጋሪ@ ….. ጠፍቶ ይሆን? እውነት ግን የአሁን ዘመን ወገኖች አብዛኞቻችን ስለ ቀደምት የኢትዮጵያ ባለውለታዎች እናውቅ ይሆን? ታዲያ ለልጆቻችንስ ማን አስረዳቸው ?ለማንኛውም ከተረዳሁት ጥቂቱን ልመስክር ፡፡

Thursday 5 December 2013

leyu leyu ልዩ ልዩ


ኢትዮጵያ እና ሩሳሌም ግንኙነት
ሩሳሌም ነገረ እግዚአብሔር በብሉይ ሆነ በዘመነ ክርስትና በስፋት የተገለጠባት ቅድስት ሀገር መሆኗ ይታወቃል፡፡ ሀገራች ኢትዮጵያም ከኢየሩሳሌም ሆነ ከሌሎች ቀደምት ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት በስፋት የሚነግረን የመጀመሪያው ማስረጃ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአምልኮተ እግዚአብሔር የኖረች በርካታ ድንቅ ነገር የተመሰከረላት ስለመሆኗ እና የመሳሰለውን መጽሐፍ ቅዱስ ከ 41 ጊዜ በላይ በመጥቀስ ገልጾታል፡፡ መዝ 67*31
ከክርስትና በፊት በብሎይ ኪዳን እምነትና ስርዓተ አምልኮ ከኢየሩሳሌም ቀጥሎ ሕገ ኦሪትን በመቀበል ሁለተኛዋ ሀገረ እግዚአብሔር የሆነችው ኢትዮጵያ ከተጓዳኝ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ጋር የነበራት ግንኙነት ምን ጊዜም ሲዘከር የሚኖር ታሪካዊ ነው፡፡ ግንኙነቱም ይደረግ የነበረው
+ የብሉይ ኪዳን እምነትና ሥርዓተ ትውፊት በመጋራት

+ በዓመት አንድ ጊዜ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ላይ በመገኘት  የፋሲካን   በዓል በህብረት በማክበር
+ አንድ ዓይነት ሕግ መጽሐፋዊ ተጠቃሚ በመሆን እና በመሳሰሉት ነው፡፡
ይህም ግንኙነት የሀገር ርቀት ሊገታው በማይችለው ሂደት ላይ የቱን ያህል ጸንቶ የኖረና የሚኖር መሆኑን ከታሪክ ብቻ ሳይሆን በአሁኑም ዘመን ጎልቶ ከሚታየው የባሕል ግንኙነት ለክብረ በዓል በርካታ ምዕመናን መጓዝና የዴር ሱልጣን ሁኔታ ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ኢትዮጵያም የመጀመሪያዋ የውጭ ግንኙነት ያረገችው ከኢየሩሳሌመ ጋር መሆኑንም ያመለክተናል የንግስቲቱ ጉዞ ቀድሞም ሀገራቱ ግንኙነት እንደነበራቸው ማስረጃ ነው፡፡

Tuesday 10 September 2013

5ቱ ስጦታዎች (ክፍል 2)

4.በኩራት
በኩር ማለተ የመጀመሪያ ማለት ሲሆን የበኩራት ስጦታ ከልጅ፤ከከብት፤ከንብረት… ከመሳሰለው የመጀመሪያውን መስጠት ነው፡፡የአዳም ልጅ አቤል መስዋዕት ሲያቅርብ ‹‹ የመጀመሪያውን ለየ›› የሚለው በኩራቱን ስለማቅረቡ ሲያስረዳ ሲሆን፡ ይህም የተወደደ መሥዋዕት ሆኖለታል /ዘፍ 4፤4/ ፡፡ከዘመነ ኦሪት ጀምሮ ሕዝበ እግዚአብሔር  አምልኮታቸውን ከሚገልጹበት አንዱ በኩራት ነበር፡፡ከልጆቻቸው፤ከምርታቸው.... በኩር  የሆነውን ለእግዚአብሔር ቤት ይሰጣል፡፡ /ዘኁ 3፤42፤ 1ሳሙ 2፤ ዘኁ 18፤15-17/፡፡
በኩራትን ማቅረብ እጅግ የተወደደ እና ከሁሉ የሚበልጥ የስጦታ ዓይነት ነው /ዘዳ.23÷19፤ ዘዳ.26/፡፡ክርስቲያኖችም ሁላችንም ሥርዓተ አምልኮ የምንገልጥበት አንዱ የሆነውን በኩራቱን በማቅረብ ሕገ አምላክን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ይህንንም ከመጀመሪያ ምርታችን፡ ከመጀመሪያ ደሞዛችን ለእግዚአብሔር ቤት በመስጠት የተናገረውን ከማያስቀረው አምላካችን በረከት እንደምናገኝ በማመን ልንፈጽም ይገባናል /ዘዳ28÷1-15/፡፡
5.ዐሥራት
ዐሥራት አንድ አሥረኛ ማለት ነው፡፡ከሚያገኙት ገቢ አንድ አሥረኛውን ለእግዚአብሔር ቤት መስጠትን ያመለክታል፡፡ከሙሴ በፊት በዘመነ አበው የተጀመረ የእግዚአብሔር ሕግ ነው፡፡መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት በስፋት ይገልጻል፡፡ከነዚህም ለአብነት ያህል በጥቂቱ እንመልከት፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት አበ ብዙሓን አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ መልከ ጼዴቅ በሄደ ጊዜ ዐሥራት ማውጣቱን ‹‹አብርሃምም ከሁሉ ዐሥራት ሰጠው›› በማለት ዐሥራትን አበው እነደጀመሩት ያስረዳናል/ዘፍ 14÷20/፡፡ ያዕቆብ ከአባቶቹ የወረሰውን ሕገ አምላክ የሆነውን ዐሥራት ማውጣትን ሲገልጽ ‹‹ከሰጠኸኝ ሁሉ ለአንተ ከዐሥር አንዱን እሰጣለሁ›› ብሏል /ዘፍ 28÷ 1-22/፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት ሲያስረዳን ከእግዚአብሔር የታዘዘ መሆኑን አጽንኦት በመስጠት  ነው፡፡ ‹‹ከምታገኘው ሁሉ ዐሥራትን ታወጣለህ›› የሚለው ‹‹ዐሥራት አስገቡ›› ማለቱ እነደዚሁም የምድር ዐሥራት የእግዚአብሔር መሆኑን የሚገልጹ ማስረጃዎች ሁሉ ዐሥራት ሕገ አምላክ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡ /ዘዳ. 14÷22፤ ዘሌ.27÷30፤ ዘዳ.12÷17፤ ዘዳ.14÷23፤ ሚል.3÷10/፡፡
መድሓኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ ‹‹የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ስጡ›› ማለቱ አምላካዊ ትዕዛዝ መሆኑን ያስገነዝበናል /ማቴ 22÷17/፡፡እንደዚሁም አንድ ቀራጭ ወደ ጌታችን ቀርቦ ‹‹ከማገገኘው ዐሥራት አመጣለሁ›› ማለቱ ቀድሞ የነበረ ሕግ መሆኑን የሚያመለክት ሲሆን ጌታችንም ቀራጩን በዐሥራት ጉዳይ ላይ መልስ አለመስጠቱ ዐሥራት ተገቢ የሆነ ሥርዓት መሆኑን የሚያመለክት ነው /ሉቃ 18÷12/፡፡

ዐሥራት በመስጠታችን የምናገኘው ጥቅም ምንድን ነው?

Thursday 22 August 2013

5ቱ ስጦታዎች

ሥርዓተ አምልኮ ከሚገለጥበት መንገድ አንዱ ስጦታ ነው፡፡ የሰው ልጅ ከራሱ የሆነ አንዳች የለውም በጎ የሆነው ሁሉ ከፈጣሪ ዓለማት ከእግዚአብሔር ያገኘው ነው፡፡ በመሆኑም ፈጣሪያችን መስጠትን እንዳስተማረን ሁሉ እኛም ተገዥነታችንን ከምንገልጥበት አንዱ ከርሱ የተቀበልነውን በፈቃደኝነት በደስታ በመስጠት ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት ይህን ሲያስረዳ ‹‹ሁሉ ከአንተ ዘንድ ነውና፡ ከእጅህ የተቀበልነውን ሰጥተንሃልና ይህን ያህል ልናቀርብልህ የቻልን ማነን? .. በፈቃዴ ይህን አቅርቤአለሁ›› በማለት ከእግዚአብሔር ያገኘውን ሀብት በደስታ በፈቃዱ ለቤተ መቅደስ ሥራ እንዲውል መስጠቱን በመግለጽ ስለ ስጦታ ጽፏል /1ዜና 29÷9-16/.
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ነገር ግን ሁሉ በአግባብና  በሥርዓት  ይሁን›› በማለት እንዳስተማረን ለእግዚአብሔር የምንሰጠውን የአምልኮ መግለጫ በሥርዓት ልናደርገው እና ከልብ  ሊሆን ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ መሠረቱ  የስጦታ ዓይነቶችንና የአቀራረብ ሥርዓቱን ማወቅ ነው፡፡በዚህች አጭር ጽሑፍም በሥርዓተ ቤተክርስቲያን መሠረት መንፈሳዊ ምግባራት የሆኑት አምስቱ የስጦታ ዓይነቶች ምጽዋት፡ መባዕ፡ ስዕለት፡ በኩራት እና ዐሥራትን እንመለከታለን፡፡

Thursday 18 July 2013

ምክረ ካህን



“መፋታትን እጠላለሁ ”ሚል 2÷16

ጋብቻ እግዚአብሔር የፈቀደው ክቡር ነው በይበልጥም በስርዓተ ቤተክርስቲያን በንስሐ እና በቅዱስ ቁርባን የሚፈፀም ጋብቻ ቅዱስ ጋብቻ ነው፡፡ ኤፌ 5÷32 ማቴ 19÷5 ሆኖም ግን ጋብቻ የበዛውን ያህል ፍቺም እየበዛ መሆኑ ግልፅ ነው በርካቶችም ወደ ፍቺ የሚያመራ ትዳር ውስጥ እንደሚገኙ ይናገራል ስለሆነም በዚህ እትም በምክረ ካህን ዓምድ የፍቺ ምክንያቶችና ፍቺ እንዳይገጥም መፍትሔዎችን በጥቂቱ እናስነብባለን፡፡
እግዚአብሔር ፍቃዱ በጽናት እንድንኖር ነው እንጂ ፍቺን እንደሚጠላ “መፋታትን እጠላለሁ” የሚለው አምላካዊ ቃል ያስረዳናል፡፡ ከጋብቻ በፊት የመጠናናት ዓላማ ክፉ፣ደግ ጠባያቸውን ለይተው ተቻችለው ለመኖር መሰረት የሚጥሉበት ነው፡፡ ሆኖም ግን አንዳንዶች በአግባቡ ሳይጠናኑ ወይም ስለ ጋብቻ ኑሮ በቂ ግንዛቤ ሳይኖራቸው ወደ ትዳር ሲገቡ ከመኖር ይልቅ ፍቺ ሲገጥማቸው ይታያል በርግጥ በዝሙትና በሀይማኖት ልዩነት ፍቺ ሊኖር እንደሚችል ይታወቃል ከተስተካከሉ ወይም ችግራቸውን ካስወገዱና ከተስማሙ ከፍቺው ይልቅ አብሮ መኖር የተመረጠ ነው፡፡ ሉቃ 16÷18   ማቴ 19÷9
በዘመናችን በርካቶችን ለፍቺ የዳረጉ ነገሮች ምን ይሆኑ?

Friday 12 July 2013

ነገር በምሳሌ….



በግ በውሻ ቀና
ሊቁ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ስኳርና ወተትየሚል ከእንግሊዘኛ የተተረጎመ በ1922ዓ.ም ከፃፉት ተረት መጽሐፍ ላይ የጠቀሱትን እንመልከትና እንማርበት፡፡ ምሳሌ ማስተማሪያ መንገድ ነው፡፡
ብዙ በጎች ያሉት አንድ ሰው ነበር እርሱም በጎቹን ሲጠብቅ በብዙ ጥንቃቄ ነው፡፡ የለመለመ ሳር ይመግበቸዋል፣ የጠራ ውሃ ያጠጣቸዋል ሲመሽም ወደ ጉሮኗቸው ያስገባቸዋል፡፡ በዚህ መልኩ በጣም ይንከባከባቸዋል፡፡ ከአንዱ ግልገል በቀር ሁሉም ጠባቂያቸውን ይወዳሉ፡፡ ያ አንዱ ግልገል ግን ጠባቂውን አይወድም፡፡ አንድ ቀን ወደ እናቱ ቀርቦ እናቴ ሆይ እኛ ማታ ማታ ለምን ይዘጋብናል እነሆ ውሾች ሳይዘጋባቸው እየተጫወቱ ያድራሉ፡፡ እኔም ከአሁን በኃላ እንደ ውሾች ማታ ማታ መጫወት እፈልጋለሁኝአላት፡፡ እናቲቱም ልጄ ሆይ አርፈህ ተቀመጥ ጠባቂያችን እጅግ መልካም ነው እርሱ እንዳዘዘን ውለን ብንገባ ይሻለናል፡፡ እንቢ ያልክ እንደሆነ በራስህ ላይ ጥፋት ታመጣለህ አለችው፡፡ 

ሐዋርያት



ሐዋርያ የሚለው ስያሜ ሖረ፣ሔደ ከሚለው ከግዕዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጉሙ የተላከ፣ሒያጅ፣ልዑክ ማለት ነው፡፡ ይህ መጠሪያ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማስተማር ዘመኑ ከተለያዩ ተግባራት እንዲከተሉት ከጠራቸው ለ12 ደቀ መዛሙርት የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡ ማር 3÷13 በኃላም ወንጌልን እንዲሰብኩ “ሑሩ ወመሐሩ” ብሏቸዋልና ሐዋርያት ተባሉ፡፡ ማቴ 28÷19 ቅዱሳን ሐዋርያትም ከድሆች፣ ከሀብታሞች፣ ከምሁራን፣ ካልተማሩ ወገኖች ሲመርጥ ለዓለምም ክብር እንዲያጎናጽፉ የበረከት መልዕክተኞች የዓለም ጌጦች አድርጓቸዋል፡፡


Tuesday 2 July 2013

እየሩሳሌም


            “እየሩሳሌምን በልባችሁ አስቡ” ‹‹.ኤር 51÷51››
ነቢዩ ኤርምያስ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ539 ዓ/ዓለም ገደማ ስለኢየሩሳሌም ነፃ መውጣት እና ስለ ባቢሎን መፍረስ የተናገረው ነው፡፡ ፍፃሜውም በኢየሩሳሌም ስለሚፈጸመው ነገረድኅነት እና ከክርስቲያኖች ልብ የማትጠፋ ሀገር ስለመሆኗ የሚያመለክት ነው፡፡
እስራኤል
አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ለይስሐቅ ልጅ ለያዕቆብ የሰጠው ስያሜ ነው፣ ካልባረከኝ አልለቅምህ ብሎ ነበርና “ከእግዚአብሔር ጋር ይታገላል ያሸንፋል” ሲል እስራኤል አለው፡፡ ዘፍ. 32÷22 በኋላም የያዕቆብ ልጆች የተጠሩበት እና ከሰሎሞን በኋላ ዐሥሩ ነገዶች ያቋቋሙት የሰሜናዊው ግዛት (መንግሥት) ስያሜ ሆኗል፡፡ ዘፍ 49÷7 ዘዳ 14÷39 1ኛ ነገ.12÷16
 በአዲስ ኪዳን የክርስቶስ ተከታዮች እስራኤል ዘነፍስ ተብለዋል ሮሜ. 9 ገላ. 3÷6 ሮሜ. 4÷12
እየሩሳሌም
ኢየሩሳሌም ማለት መሠረት ሠላም፣ ሀገረ ሠላም፣ የሠላም ምልክት…. ማለት ነው፡፡ ስትጠራም የእግዚአብሔር ከተማ፣ ቅድስት ከተማ፣ የዳዊት ከተማ ተብላ በቅዱሳት መጻሕፍት ተጠቅሳለች ንጉሠ ሰላም የተባለው የጌታችን ምሳሌ ሆኖ የሚነገረው መልከፄዴክ እንደመሠረታት ይነገራል፡፡ ዘፍ. 14÷ ነህ. 11÷1 የአበ ብዙኃን አብርሃም የልጆቹ፣ የበርካታ ነቢያት ሀገራቸው ፣ ታላቁ ንጉሥ ቅዱስ ዳዊትም ከኢያቡሳውያን ማርኮ ከተማው ያደረጋት በመሆኗ የነቢያት ትንቢት ፍፃሜ አግኝቶ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከልደት እስከ ዕርገት የኖረባት፣ ሐዋርያት የተጠሩባት፣ ነገረድኅነት የተፈፀመባት በመሆኗ በእውነትም ቅድስት ሀገር ናት፣ በማዕከለ ኢየሩሳሌም ጽርሐጽዮን የሰሎሞን ቤተመቅደስ፣ ከጲላጦስ አደባባይ እስከ ቀራንዮ መከራ መስቀል የተቀበለባቸው ቦታዎች ይገኛሉ፡፡